Showing posts with label መጽሐፍት. Show all posts
Showing posts with label መጽሐፍት. Show all posts

Mar 20, 2022

<የዘውግ ፖለቲካ ሥረ መሰረቶች>

(አጭር የመፅሐፍ ዳሰሳ)

•የመፅሐፉ ርእሥ:- የዘውግ ፖለቲካ ሥረ መሰረቶች

•ፀሐፊ :- መስከረም አበራ::

•የገፅ ብዛት 424: 
•ማንኩሳ ማተሚያ ቤት: 
•ዋና አከፋፋይ ጦቢያ:: 
•2013 ዓ.ም :: 



[መግቢያ::]

የጥናት ፅሑፍ፣ ንድፈ ሃሳባዊ እይታ ነው:: በችኮላ የተፃፈ አይደለም:: ብዙ ተደክሞበታል:: ወደ 400 የሚደርሱ የኅዳግ መዘክሮች ለዚህ testimonials (ምስክሮች) ናቸው:: 

የማንነትን ትርጉም ለመፈተሽ ምዕራፍ አንድ የዓለምአቀፍ አጥኚዎችን የጥናት ውጤቶቻቸውን እና መዛግብቶቻቸውን ከሥረ መሰረቱ ዋቢ አድርጓል:: 

ዘውግ፣ ኃይማኖት፣ መደብ፣ ባሕል  በአብዛኛው የማንነትን ብያኔዎችን ሲያግዙ እንደሚስተዋሉም እስከ ገፅ 62 ድረስ እናነባለን:: 

ፀሐፊዋ በእውቀት ጥማት ሥር በጥናት እና ምርምር እንዲሁም ለንባብ ባላት ብርቱ ውስጣዊ  መግፍኤ የተለያዩ ድንጋጌዎችን ወደ ሳይንሳዊ መዛግብት ማማተሯ በጉልህ የሚታይ ነው:: ለአንባቢም የሚበጀው ከስሜት የፀዳን የንድፈ ሃሳብ አረዳድ ታጎናፅፍለታለች:: ይህም ለአገራችን የወደፊት የተግባቦት ፖለቲካ ትርጓሜ እንደ በጎ አሻራ ( legacy) የሚሆን ነው:: በትውልድ ተስፋ የሚጣልበት በነፃነት የዜጎች ምሳሌ ነው:: 

[ጭብጥ::]

የዘውግ ሳይናዊ ትርጉሞች:- የሚለው ክፍል በገፅ 69  <<ሰዎች በተመሳሳይ ዘውግ ናቸው ማለት በጋርዮሽ የሚጠሩበት ሥያሜ አለ ማለት ነው>> ለእነዚህም ከአንድ ዘር ሐረግ የሚመጡ አፈታሪክ ያስፈልገዋቻል:: 

ለስምምነት እጅግ የሚያዳግተው ይህ አፈ ታሪክ ከእውነትነቱ ይልቅ ወደ ልብ ወለድነቱ የሚያመዝን በመሆኑ ከሳይንሳዊ ብያኔ የሚያርቀን እንደሆነ ትጠቅሳለች::

ምናልባት ለወደፊት የሚመጣው ተከታታይ ትውልድ ሳይንስን እንደ መነሻ መግባቢያ አውድ የሚወስዱት ከሆነ የዘር ሐረግን የሚፈትሹ የማስረጃ ውጤቶችን በመመልከት የዘውግን ጡዘት ሊያበርዱበት የሚችሉ እንደሚሆን አመላካች ይመስላል:: እንጂ አሁን ባለው የዘውግ አጣብቂኝ አመለካከት እውነት ኹሉ በዘውግ ልኂቃን ንግርቶች ተወስኗል:: Futile የመዳረቅ ክፍል እንጂ ተቀምጦ ለመደራደር አዳጋች ነው:: 

ማንነቶች ትገልፀው ወደ ተልያዬየእርከን ደረጃ ሲደርሱ በትኩረት የዘውግ ማንነት ጡዘት፣  ከቋንቋ ባህል እና ምጣኔ ሀብታዊ ሰልፍ ጋር ሲያዛመድ የዘውግ ፖለቲካን ይዞ ብቅ ያላል:: ከገፅ 84 ጀምሮ የዘውግ ፖለቲካ ጅማሮ በአፍሪቃ ርዕስ በስፋት ይከተላል:: 

በቡድን የሚኖር ማህበረሰብ እንዳለ ኹሉ በግለሰብ ልእልና ላይ የዳበረ እሴት ያለው ማህበረሰብ አይጠፋምና ፀሐፊዋ በዚህ ደረጃ የሁለቱን ማንነቶች አመጣጥኖ ማክበር እንዳለብን እና አንዱን ከሌላው ነጣጥሎ መሄድ እንደሌለብን ከጅምሩ ትመክራለች:: ገፅ 84::

ለአፍሪቃ የዘውግ ማንነት ፖለቲካዊ ይዘት የቅኝ ገዥዎች ድርሻ ሰፊ እንደሆነ ታትታለች:: በተለይ በግልፅ እንደሚታወቀው ቅኝ ገዥዎች በአፍሪቃ ምድር ላይ የከተማ መስፋፋትን እና የመደብ ቅርፅን በሚያሳልጡበት ወቅት አስቀድመው የበየኗቸውን የዘውግ ማንነቶች ይዞ ለመቀጠል እንደተገደዱም (እንድስገደዱ?)  ትናገራለች:: ይህንን ጉዳይ የቤተዘመድ መረብ ስትል በገፅ 86 ላይ እናነበዋለን::  በመፅሐፉ ዳሳሽ ምልከታ ምናልባት መረቡ እንደ ወጥመድ የሚተረጎም ሳይሆን አይቀረም:: 

በተፈጥሮ ሊካድ የማይችለው ዘውጌ ማንነት ልቦለዳዊ ትርክቶች፣ በጥቅም እና በቅኝ ገዥዎች መስመር የተበየነው <<ዘውጋዊ ማንነት>> ወደ ትምክህተኝነት እና ዋና አሳሳቢ ወደ ሆነው ብሄረተኝነት ትርጓሜ ያመራናል:: 

ምንም እንኳ የሥነ ፍጥረት ሳይንስ (biology) በሰው ልጆች መካከል የበየነው መከፋፈል የሰው ልጅን አንዲገዳደል ፣ እንዲጋጭ እንዲገለል ኢፍትሀዊነትንም እንዲያስከትል የሚያስችል ትርጓሜን እንደማያመጣ በገፅ 94 ተገልጿል:: 

እንደ አጠቃላይ <<ብሔርተኝነት>> በምድር ላይ  ያለው ዕድሜ ከዘመናዊው የዓለም ታሪክ ጋር መሳ ነው በሚል  ይወሰዳል::  ቃሉ በኢትዮጵያ ምናልባትም የሚታወቀው ግለሰቦች የመጡበትን የትውልድ ሐረግ ማለትም ዘብሄረ ዘጌ ፣ ዘብሄረ ቡልጋ ፣ ዘብሄረ ጎንደር በሚል ሲጠቀስ የሚስተዋለው ትርጓሜ ብሄር ከመነሻው natio ከሚለው የላቲን ቃል በቀጥታ ትርጉሙ የትውልድ ቦታ እንደሚል እንገነዘባለን:: 

ይህ እሳቤ በ16ኛው ክፍለ ዘመን ከነገረ መንግስት nation state ምስረታ ጋር ወደ ሰው ልጅ ታሪክምሆነ የእውቀት ቋት መግባቱን እናያልን:: ምናልባትም የብሄር ትርጓሜ እና የአውድ አገላለፅ ከእኛ አገር ተጨባጭ ታሪካዊ ሂደት አንፃር ሰፊ ትንታኔን እና መግባባትን የሚጠይቅ ነው:: 

ፕ/ር መስፍን በዚህ ዙርያ የኢትዮጵያ ታሪክ ምሁራንን አጥብቀው የሚሞግቱብት ርእሰ ጉዳይ ነው:: state, empire, nation እና መሰል ቃላት ወደ ነባራዊው ታሪካዊ እና ፖለቲካዊ ትርጓሜዎች ሲታዩ <<አቻ ፍቺ>> በትርጉም ደረጃ ስለሚፈልጉ ነው:: 

አውሮጳውያን በበየኑት የእነዚህ ቃላት ትርጓሜ መሰረት ከሩቅ ምስራቅ እና አፍሪቃ የረዥም ታሪክ ቁርኝት አንፃር እንዴት ይተያያሉ? የሚለው ጥልቅ ምርምን የሚጠይቅ ነው:: መስከረም ምናልባትም ይሄንን ጉዳይ በምን መልኩ እንደተመለከተችው ከገፅ98 ጀምሮ እስከ ገፅ 110 የነገዳዊነት ትርጉም ርእስ  ድረስ የምንዳስሰው ይሆናል::

እንደ ፀሐፊዋ ዝርዝር ሂደት በእንግሊዞች እና ፈረንስዮች ዲያሌክቲካዊ መርህ መስፈርት እንግሊዝ የነገረ መንግስት እሳቤ ጀማሪ ስትኾን፣ 

ፈረንሳይ የብሄርተኝነት እሳቤ አመንጭ ናት(ገፅ 99) :: በመፅሐፉ ዳሰሳ መሰረት የthesis እና antithesis ዓለም አቀፋዊ ደባ በዝርዝር ሊጠና የሚገባው ነው::

ከፈረንሳይ አብዮት ማግስት የነገረ መንግስት ትርጓሜን በብሔር እና መንግሥት በሚል አንጓ ተከፈለ:: በዚህ ርእስ ውስጥ የምናገኜው የብሔርን ፖለቲካዊ ፅንሰ ሃሳብ አጠቃላይ ውልደት ሲሆን በአንድ ነገረ- መንግስት የሚኖሩ ህዝቦችን የተለያዬ ባህል ያላቸውን ህዝቦች የሚገልፅ ቃል ነው:: 

እነዚህ ህዝቦች ፖለቲካዊ ማንነት ካለው "መንግሥት" ከሚባለው አካል ጋር ቁርኝት እንደሚፈጥሩ ተቀምጧል:: በመንግስቱና በብሔሩ መካከል ያለው ቁርኝት ብሄራዊ ተብሎ የሚገለፀውን ማንነቱን ከባህላዊ ልዩነቱ ሳያስቀደም በነገረ መንግስቱ ውስጥ የሚኖረው ትርጉም የብሄርተኝነቱን እሳቤ <<የሲቪክ ብሄርተኝነት> ስያሜን ያሰጠዋል::

እንደ መስከረም መፅሐፍ አገላለፅ የሲቪክ ብሄርተኝነት የመጀመርያ ቢሆንም በፅንሰ ሃሳብ ደረጃ የተለዬ ቋንቋን መናገር፣ ወይንም የተለያየ ባህልን ከሚያስተሳስረው የዘመናችን የብሔርተኝነት ጭብጥ ጋር አብሮ እንደማይሄድ ያሳያል:: ይህ ነጥብ በእጅጉ ውይይት የሚያስፈልገው እና በትርጉም ደረጃ ከአገራችን ታሪካዊና አሁናዊ እይታ ጋር ሊፈተሽ የሚገባው ያልነው ነው:: ምናልባትም ይህንን አጥንቶ አቅጣጫ ያስቀመጠ የልኂቅ ስብስብ ለቀጣዩዋ ኢትዮጵያ እጣፈንታ የበኩሉን የሚወጣ ባለውለታ ነው:: 

በቋንቋ እና በባህል የሚተረጎመው የዘውግ ብሄርተኝነት ከሲቪክ ብሔርተኝነት በተለዬ አንድ አይነት የሚናገሩ ህዝቦች ብሔር/ ዘውግ ተብለው መጠራት ጀመሩ:: እነዚህ ብሔሮች በጀርመን ምሁራን አመለካከት መሰረት ሃገርን የሚመሰርቱት ብሄረሰቦች ወይንም ዘውጎች ሰው ሰራሽ ሳይሆኑ ተፈጥሮአዊና መሰረታዊ ናቸው ብለው ያትታሉ:: እዚህ ላይ አሻሚ የሆነው የብሔር ቃል ወደ ብሔረሰብ አቻ ፍቺው ሆኖ መቅረቡ በጥንቃቄ ሊፈተሽ የሚገባው ነው:: ብሔር ምንድን ነው? ብሔረሰብስ? 

በገፅ 100 ላይ የምናገኜው የሲቪክ ብሔርተኝነት ቃል በ102 ገፅ ላይ "በሲቪክ ብሄረተኝነት" ቃል መተካቱ የትየባ ስህተት ወይንስ ብሄርተኝነት/ብሄረተኝነት ጋር ተመሳሳይ ትርጉም ነው የሚለው ግልፅ አይደለም::

ብሔር፣ ብሔርተኝነት ከዘውግ ስሜት ጋር ብቻ ታይቶ የሚቀርብ ባለመሆኑ ከፍተኛ ትኩረት እና ምርምርን የሚጠይቀው ለምንድን ነው ቢባል በሃገረ መንግስት ምስረታ ሂደት ውስጥ የራስን ሪፐብሊክ እስከ መመስረትን የሚያልምፖለቲካዊ እንቅስቃሴ በመያዙ እንደሆነ በመፅሐፉ በገፅ 103 ላይ ይገኛል:: ብሔርና ብሔረተኝነት የሕልውና ጉዳይ ነው:: 

በአጠቃላይ ትንታኔ የብሔር ፅንሰ ሃሳብ ከመነሻው ጋር የሚስተዋለው የአገራችን ብሔር ትርጉም የአሮጳውያኑን የብሔር መስፈርት አሟልቷል ለማለት እንደሚያዳግት ትቀሳለች:: ይህ ድምዳሜ ስምምነትን ባላስቀመጠበት ሁኔታ የሃገራችን የበላይ ህግ ግን ያለ ርህራሄ መዝግቦታል:: ለዘውግ የሚቀርበው የህገመንግስቱ ትርጓሜ የማደናገርያ አካሄድ ምንጩ መሆኑን እናነባለን:: ይህ አካሄድ ኢትዮጵያን ወዳልነበረች ሃገርነት የመቀየር ኃይል እንዳለውም በዝርዝር ተቀምጧል:: ከላይ እንደጠቀስነው ይህ ኃይል አስቀድሞ በእንግሊዞች ሲታገዝ መቆየቱንም መዘንጋት የለብንም:: 

በአገራችን በሶስት ዘውግ ብሔርተኛ ልኂቃን(ኦሮሞ፣  ሱሜሊ እና ትግሬ) ዘንድ የሚቀነቀነው የመገንጠል ፍላጎት መኖሩን የምትጠቅሰው መስከረም ሁሉንም ዘውጎች ብሔር ብሎ የሚገልፀው ህገመንግስት ለምን እንደሆነ እንመርመር ትለናለች:: ጥናት አስፈላጊ መሆኑን የምታሰምረው መስከረም ዘውጎች በሕገመንግስታዊ አንቀፅ ብሔር ተብለው የመገንጠልን ለሃገረ መንግስቱ ቀቢፀ ተስፋ ማነገባቸው ሥሕተት ነው:: ገፅ 109::

በአሁኑ ሰኣት ያሉ የኢትዮጵያ ዘውጎች ወደ ፅንፉ የመገንጠል መውጪያ በር አለመታተራቸው (አለማናተራቸው) ከመነሻው ዘውጎችን በብሄር በይኖ ተገንጠሉ መባሉ የሥህተቶች ሁሉ ቁንጮ ማሳያ መሆኑንም ትሞግታለች- መስከረም::

ከዚህ ገፅ ቀጥሎም በኢትዮጵያ ውስጥ የሚታዬውን አጠቃላይ መዋቅራዊ የፖለቲካ አስተሳሰብ ስረ መሰረቱን ከአማራ ከኦርቶዶክ ቤተክርትስያን እና ከአማርኛ ቋንቋ ጋር የሚተሳሰረውን ትርክት በማስረጃዎች እና በታሪካዊ ክስተቶች እያጣቀሰች የግል እሳቤዎቿን ታጋራናለች:: 

የኢትዮጵያ ህገመንግስትም ይሁን መሰረቱ የሆኑለት የትግሬ ዘውግ ልኂቃንን ጨምሮ የኦሮሞ እና የሱማሊ ዘውግ ብሄርተኞች ከአንድ ዘውግ ጋር ባላቸው የትርጉም አይን ይመሳሰላሉ:: ምንም እንኳ የፖለቲካ አላማ በየዘመኑ የፖለቲካ ዘይቤ የሚለያይ መሆኑ ቢታወቅም (ገፅ 294) የኢትዮጵያ ነባራዊ የታሪክ ሂደትን የአንድ ዘውግ ተኮር ይዘትን ይዞ የተንከባለለ ሃገረ መንግስት እንዳልሆነ ትዘረዝራለች:: 

የአገዎች ሥርወ መንግስት በወንድማማቾቹ በላሊበላ እና በሃርቤ መካከል የተደረገው የሥልጣን ሽኩቻ ላሊበላ አማሮችን ይዞ በመሄድ ድል እንደነሳና ነገረ መንግስቱ ዘውግ ተኮር አለመሆኑን እንደ አባሪ ትጠቅስልናለች:: 

አማርኛም የቤተ መንግስት ቋንቋነቱን በአገዎች አፀና እንጂ በዘውጉ ልኂቃን ፍላጎት በጀት ተበጅቶለት እንዳልተስፋፋ ለማሳዬት ብዙ ርቀት ሄዳለች:: በተለይ ሚስዮናዊያን አማርኛን እንዲስፋፋ ከግእዝ በተቃራኒው የካቶሊክ እምነት በአማርኛ እንዲሰበክ በመሆኑ አማርኛን የአገሪቱ ዘውጎች መግባቢያ ቋንቅ አድርጎ እንደወሰደው ትሞግታለች:: በቅርብ ዓመታት የሚታዩ የብሄርተኝነት እንቅስቃሴዎችንም ትላንት ከምናስታውሳቸው ፖለቲካዊ ቀውሶች ጋር እያዛመደች የምፍትኄውን ጎዳና ትቀይስልናለች::

[መውጫ::]

የመዳኛ መንገዱንም በአጭር ገለፃ ትደመድማለች:: 

የዘውግ ብሄርተኝነትን የሚቃወሙ ግለሰቦችም ይሁኑ ይድኑበት ዘንድ በዚህ መፅሐፍ ዙርያ ብዙ ውይይት ሊያደርጉ  እንደሚገባቸው እሙን ነው:: ይህ የተሰማው ግለሰብም ይሁን - ቡድን እንደ ዘውግ ፖለቲካ ስረ-መሰረቶች ዓይነት  የሃሳብን ጉልበት ተጠቅሞ በመፅሐፍ መልክ የበኩሉን አሻራ ይወጣል:: 

ከየሱፍ ያሲን <<ኢትዮጵያዊነት አሰባሳቢ ማንነት በአንድ አገር ልጅነት >> መፅሐፍ ቀጥሎ ደጋግሜ ለማንበብ የምመርጠው  መፅሐፍ ነው::   

ኢትዮጵያችን ቸር ይግጠማት:: 

መልካም ንባብ::

ተስፋ በላይነህ:: 
መጋቢት 2013

Feb 7, 2022

ሚተራሊዮንን

ሚተራሊዮንን እንደቃረምኳት!
 
(ተስፋ በላይነህ።)



እንደተለመደው ነው። ተመሳሳይ መነሻ ጭብጥ፥ መሰረታዊ ፅንሰ ሐሳብ፥ የተራቀቀ የጉዞ ሰልፍ። እንደተለመደው ነው! 

እመጓ፣ ዝጎራ እና መርበብት በተመሳሳይ አውድ፥ በተያያዘ ይዘት እና ገፅ ባህርይ፥ ውስጣዊ ማንነታችንን /በስነልቦና ውቅር አንደበታችን ላይ/ የሚስተዋለውን ‘ደዌ’ ታሳቢ በማድረግ፤ ያለንን ከሌለን፥ የሌለንን ካለን ጋር በተቃርኖ ስሌት እያዋዛ፤ የነበርንበትን ካለንበት ፥ ያለንበትን ከነባራዊው ዓለም እንዲሁም ከመጭው እኛነታችን ጋር በማስተሳስር የአሁንን ወርቃማ እድል ፈልቅቀን እናጌጥበት ዘንድ ይማፀናል። እንደተለመደው ነው። 

ስሌት እና ብልጠት ‘መድኃኒቶቻችን’ እንደማይሆኑ በገፅ 251 ላይ የአብዛኞቻችን ገፀ ባሕርይ ሆኖ ዋጋ እያስከፈለን እንደሆነ ያመላክተናል። እንደተለመደው! 

ሚቶሎጂ ነው። ምናልባትም ሃይማኖታዊ፥ በሚያስደንቅ ሁኔታም ሳይንሳዊ ነው። በልማዳዊ አስተሳስባችን ላይ የሚዘወተሩ ተግባራትን ከሳይንሳዊ ፅንሰ ሐሳቦች ጋር እያጣመረ አጭር መግለጫ ጥሎ ያልፋል። ስዎች ተነግሯቸው ካላመኑ በተግባር ሊማሩ ግድ ነው። <<the law of Effect>> ገፅ 250።energy deception ገፅ 219። ስለ ውሃ memory ገፅ 186 አይነት ዝርዝር ምሳሌዎችን መጥቀስ እንችላለን። 

የሚተራሊዮን ውበት ጥልቅ ድረስ ከሚደርሰው ሕመሟ ጋር ተስፋን እና ቀቢፀ ተስፋን በአንድ ማዕድ እንድንሳትፍም ያደርጋል። እንደ ሀገር ያሉንን ሁሉ፥  ጥልቅ ባህር ድረስ እየቃኜ ሲያስቆጥረን፥ ባዶ ማዕድ ላይ ለመዝገን እርስ በርሳችን የሚያነካክሰንን ወስጠ መሰረት ዳሰሳም ያደርጋል። እንደተለመደው ነው።   

አንዳንዶች እመጓንም ይሁን ሌሎች የዶክተር ዓለማየሁ ዋሴን መፅሐፍት እንደ ቅዥት እና አጉል የመንጠራራት ‘ምናባዊ ዴሉዥን’ አድርገው ይቆጥሯቸዋል። የሌለንን እና ያልሆንነው እኛነታችን እየለጠጠ በባዶ ሙሊት 'የተወጠረ ፊኛ' አድርገውም ይገልፁታል። ምንም ማድረግ አይቻልም፥ እንደተለመደው ነው። 

ይህንን ሐሳብ ለመሟገት ጥንታዊ የብራና መፅሐፍትን ጥልቅ ዳሰሳ አድርጎ፥ ዘመናዊ ከሚሉት ሳይንሳዊ ትወራዎች እና ጥናቶች ጋር እያስተሳስሩ መወያዬት የወግ ነው። 

ሚተራሊዮን ልክ እንደ ቀደሙት የደራሲው ስራዎች ጉዞን፥ ቁፋሮን፥ ተፈጥሮአዊ ፀጋዎችን መዳሰስ፥ ምርምር ጥናቶችን ማቅረብ፥ ራስን መገምገም፥ ችኩልነታችንን እና ስግብግብነታችንን፥ ጥራዝ ነጠቅነታችንን እና ቆሞ ቀርነታችንን በዋና ገፀ ባህርይው አምሳያነት በራሱ ላይ ሰይሞ የችግሮቻችንን ምንጮች በቅደም ተከተል ያስቀምጣል። የችግርን ምንጭ ወደ ሌላው ሃይቅ ከመቀሰር ይልቅ ወደ ራስ ወንዝ መሻገርን ይመርጣል። ሰከላ ግሽ ዓባይ ላይ የነበረው ትዕይንት ለዚህ ገላጭ ነው።  

262 ገፆች ያሉት መፅሐፉ ልክ እንደ ጣፋጭ ማዕድ ቶሎ በልቼው ቶሎ በጨርስኩት የሚያስብል አይነት ነው። 

የኢትዮጵያን ብልፅግና አጥብቆ ይሻል። የብልፅግና መርህ /ፍኖቱንም/ ሳይሰስት ከእነድክመታችን ፥ ከእነ ጉልበታችን ፤ ከእነ ነውራችን ፥ ከእነ ጌጣችን በዝርዝር ያሰናዳል። እንደተለመደው ነው!

አይሁድ፣ እስልምና እና ክርስትና ሃይማኖቶች በኢትዮጵያ እንዴት ተቆራኝተው እንደሚኖሩ፤ ነቢል በአባይ ውሃ ላይ ያለውን ቁጭት፥ የአይሁድ እምነት መሪ የሆኑትን አባ ዮናታንን ከገዳማዊያን አባቶች ጋር ያስተሳሰረበት ዘዴ ለዚህ አመላካች ነው። 

የኢትዮጵያን ልዩ ልዩ ቀለማዊ ገፅታዎች በምን ሕብረት እና ሕብረቀለማዊ ትስስር ለመግለፅም ገፅ 259 አይነተኛ የሰበዝ አካል ነው። 

‘ጎንደሬ ፈትሎ ዶርዜ የሸመነው፥ ጥልፉን አክሱማይ ጠለፈው? አማሴን?፥ ዐይነ ርግቡን ማን ሰጣት? አፋር ሱማሊው? አንጠረኛው ማን ነው ሽናሻው? መንበሯስ ከጅማ ምድር የበቀለ ነው ሲል በወፍ በረር ያስተሳስረናል።’ 
 
ውሃ፣ ማዕድናት እና እፅዋት ፀጋዎቻችን ላይ መሰረታዊ የሃይማኖት ንባቦችን፥ ከሳይንሳዊ መላምቶች እና ሀተታዎች ጋር በማጣመር ፍንጭ ሰጪ ገላጭ መፅሐፍ በመሆኑ፤ የማይነካካው የመንግስት ተቋም ዘርፍ ባለመኖሩም ፥ የዘመኑ የብልፅግና መሪዎች ዘንድ ሊዳረስ የሚገባው ዘመንን የሚዋጅ ገፀ በረከት ይመስለኛል።  

በተለይም ለ22ቱ የመንግስት ካቢኔዎች መፅሐፉ ይዳረስ ዘንድ በስጦታ መልክ እንዲቀርብ የሚያስችል የአስተባባሪ [ኃላፊነት] ብወስድ ምርጫዬ ነው። 

በአጭሩ ለሚተራሊዮን በቀረበው ምርቃት መተርጉማን ቃላት እንሰነባበት። 
 
ውሃ፣ አፈር፣ ዕብን/ድንጋይ -ማዕድን/፣ እሳት፣ ንፋስ፣ ዘር እፅዋት የወለድሺው ይውለድሽ ፥ ይስማሙልሽ. . .! በሚል በደርዝ ተቀምጠዋል። 

እንደተለመደው ከድንቁርና ግርሻ የሚያነቃ፥ ለኔ ብጤ ድውያን ፈውስ ነው! እንደተለመደው ነው። 

መልካም ንባብ!

Feb 26, 2021

በዕውቀት መገበያዬት!

የመፅሐፍ ዳሠሳ::


የመፅሐፉ ርእስ:- <<ሪስ እስቴት ኢንቨስትመንት አስተዳደር እና ግብይት>>


ፀሐፊ:- ደሳለኝ ከበደ (Eng: MSc, MBA-IB]


የመፅሐፉ ገፅ ብዛት:- 234



በአንድ ሙያ ዘርፍ ልምድን እውቀትን እና ጥልቅ

ግንዛቤን ያካበቱ ግለሰቦች ስለሙያው መፅሐፍ 

ሲፅፉ ተሽቀዳድሞ የማንበብ ልማድ አለኝ:: 


ደሥታዬም ወሰን አይኖረውም:: ምክንያቱም ብዙ አመታትን ተምሬ ገንዘብ ከፍዬ የምማረውን 

ትምህርት በምወደው ሥነ ፅሑፍ ዘርፍ ንባብ [መፅሐፍመልክ ተከሽኖ ሲገኝ የደሥታዬ ዓቢይ ምክንያት ነው:: 


ይህንን የምለው የካቲት ወር 2013 . ለንባብ የበቃውን የኢንጅነር ደሳለኝ ከበደ 

<<ሪስ እስቴት ኢንቨስትመንትአስተዳደር እና ግብይት>> በሚል ርእስ የታተመውን 

የሙያ ነክ የንግድ ምክረ ሐሳብን የያዘ 

መፅሐፍ ለገብያ ሲወጣ ነው::


አንድ መፅሐፍ በተለምዶ በተደጋጋሚ የምናውቀውን ድርጊት 

ሥሕተት መሆኑን አርሞ ትክክለኛውን ትርጓሜ እና

አቅጣጫ ሲያስቀምጥልን በረከቱ ሁለንተናዊ ነው:: 


ይህንንም የምናዬው በመፅሐፉ  ጅማሬ ላይ እንዲህ በሚል ይነበባል:: 


[...] አንዳንዶች ግንባታን እና የሪል እስቴት ልማትን አንድ አድርገው ሲገልጹ ይስተዋላል:: ይህ ግን ስሕተት ነው::  ገፅ 3


[...] የሪል እስቴት ልማት ሥራ የሂሳብ እና ገንዘብ ነክ ባለሙያዎችን  

የሕግ ባለሙያዎችን  የፕሮጄክት ትግበራ ባለሙያዎችን  

የግንባታ ሥራ መሪዎችን  የተለያዩ የዲዛይን ሥራ የሚሠሩ ባለሙያዎችን  

የሕንጻ አስተዳደርሥራ አዋቂዎችን  

የሽያጭ እና 

ገበያ ጥናት ሥራ የሚሠሩ ሙያተኞችን የመሣሰሉትን ያካትታል:: ገፅ 3


እንግዲህ መፅሐፉ በዚህ አይነት ቅኝት  

ሥሕተትን እየነቀሰ በማውጣት 

የባለሙያ ሐተታዎችን እና 

ዝርዝር ትንታኔዎችን 

ቀለል ባለ አማርኛ ያቀርብልናል:: 


በሃገራችን ረዥም ታሪክ  የሚታወቁትን ቁሳዊ ቅርሶችንም በመጥቀስ 

የሪል እስቴት ታሪክ አመጣጥን ትርጓሜን 

በመግለፅ እንዲሁም ሌሎችን 

ዝርዝር ሐሳቦች ከአገራችን ነባራዊ ሁኔታ ጋር ለማስተሳሰር ይሞክራል:: 


የሪል እስቴት ኢንቨስትመንት ሰፊ 

የኢንቨስትመንት ዘርፍ ከመሆኑ ጎን ለጎን 

ዘርፈ ብዙ ባለሙያዎችን 

እና ባለድርሻ አካላትን እንዲሁም 

ለኪሳራ የሚያጋልጡ ተጓዳኝ የጎንዮሽ 

ተፅእኖዎችን የሚያስተናግድ ሆኖ በመገኜቱ በሚጠበቀው ልክ 

ስኬታማ አለመሆኑን እንገነዘባለን:: 


ይህም በቁጥር ሲገለፅ ለምሳሌ 

1481 የአገር ውስጥ ባለሀብቶች 

በሪል እስቴት ፕሮጄክት ውስጥ የተመዘገቡ መሆናቸውን ገልፆ

 3.4% ማለትም 50ዎቹ ብቻ እየተሰሩ ፤ 

60ዎቹ ደግሞ ወደ ተግባር እንቅስቃሴ መግባታቸውን ይገልፃል:: 


የውጭ ባለሃብቶችን የሚያሳትፍ ዘርፍ ከመሆኑም ጋር ተያይዞ  

እስካሁን 6% የሚሆኑ የውጭ ባለሀብቶች የተመዘገቡበት ነው:: 

ገፅ 164


ከዚህ ጋር ተያይዞ ለውጭ ባለሃብቶች አገራችን ያስቀመጠችው የገንዘብ መጠን እና የመሬት ስፋት ከሌሎች አገራት አንፃር ሲታይ 

እጅግ ዝቅተኛ መሆኑም ተቀምጧል:: 

ገፅ 180


መፅሐፉ አጠቃላይ የሪል እስቴት ዘርፍን ከታችኛው መዘጋጃ ቤታዊ አገልግልቶች ችግር (ገፅ 165) ጀምሮ እስከ ላይኛው ዝርዝር የመንግሥት ተቋማት ጋር በማዛመድ የዘርፉ ተግዳሮቶችን 

በግልፅ ቋንቋ ዘርዝሮ አስቀምጧል:: 


በሪል እስቴት ዘርፍ ለመሰማራት 

አስፈላጊ የሙያ ትንተናዎችን 

የሚያካትተው መፅሐፉ በዚህ ንግድ ዘርፍ ሊሰማሩ የሚያስቡ ግለሰቦች 

(በጋራ ቢሆን ይመክራል - ገፅ 203) የመግቢያ በሩን በተደላደለ የእውቀት መርህ ስር እንዲዋቀር የሚረዳ ፈር ቀዳጅ ሥራ ፍኖተ ካርታ ሆኖ የሚያገለግል ነው::


በአገራችን እንደዚህ አይነት የንግድም ይሁን የትኛውም ዘርፎች 

ውስብስብ የሆኑ የአስተዳደር ሂደቶችን የሚጠይቁ ከሆኑ ከስኬታማነታቸው 

ይልቅ በጅምር ሲቀሩ ለከፋ ኪሳራ 

እና ለግለሰባዊ ለአካባቢያዊ 

ምስቅልቅሎች 

ስንዳረግ በተደጋጋሚ የምናስተውለው ሐቅ ሆኗል:: 


ፕሮጄክት አፈፃፀም ላይ የሚስተዋለው 

ክሽፈታችን የትኛውንም የሙያ ዘርፍ 

በቂ ልምድ ክትትል እና ሙያተኞችን 

የማያሳትፍ የስራ ቅንጅት አለመኖሩን 

የሪል እስቴት መፅሐፍ በሚገባ ያሳየናል:: 


የመሬት አቅርቦቱ  የቀረጥ ነፃ ማበረታቻ  

መንግስት ከግለሰቦች ጋር በጋራ ቢሰራ በሚል የተቀመጡት ምክረ ሀሳቦች 

ፀሐፊው በሙያው ያካበተውን 

የቆዬ የስራ ልምድ ታሳቢ የሚያደርግ ጥቆማዎች አሉት:: ገፅ 190/191


<< አብዛኞቹ የሪል እስቴት ፕሮጄክት አልሚዎች የግንባታ ሥራ 

የሚያከናውኑት እንደ ሪል እስቴት 

አልሚ ባለሀብት ተመዝግበው  

የሪል እስቴት ንግድ ፈቃድ ኖሯቸው 

ሳይሆን የሕንጻው ግንባታ ፈቃድ ብቻ 

አውጥተው ግንባታ የሚያከናውኑ በመሆናቸው ነው::


አብዛኞቹ  የሪል እስቴት አልሚዎች ወደ ሪል እስቴት ሥራ ምዝገባ የሚገቡት  

የመጠቀሚያ ፈቃድ አውጥተው 

ለማከራዬት ወይም ለመሸጥ 

በሚያስቡበት ወቅት ነው>> 

ገፅ 163 ::


ይህ አካሄድ ለጥናት ምቹ አለመሆኑን እና ዘርፉን በሙያዊ እይታ የተለያዬ ተጨማሪ 

ችግሮችን ማስተናገዱን ይጠቅሳል:: 


በአጠቃላይ መፅሐፉን በዘርፉ ሊሰማሩ ላሰቡ ድርጅቶች "አጤሪራ" ቋሚ ማስታወሻም ተይዞለት የሚነበብ ነው:: 


የእውቀት እና ክህሎት ልምምድን 

በቅድሚያ ታሳቢ በማድረግ 

የንግድ ባህላችንን ጥናታዊ 

ሂደትን የሚያበረታታ 

ወቅቱን የጠበቀ በብዙዎች 

የአገራችን ክፍል

ለውይይት ቀርቦ እገዛውን በተጨባጭ ሊያረጋግጥ የሚገባው ነው:: 


የመፅሐፉ አላማ የሪል እስቴት ዘርፍ በነዋሪው ሊገዙ የሚችሉ  (Afordalbe houses) 

እንዲበራከቱ የሚጥር 

በመሆኑ ምናልባትም ፀሐፊው 

በተካነበት ሥልት ለቀጣይ ተያያዥ 

ሥልጠናዎችን

ለመስጠት የተዘጋጄበት ትጋት በድጋሚ የሚያስመሰግነው ነው:: 





በፕሪፋብ (ተገጣጣሚ የቤት አይነቶች

ላይ የደረሰውን የተጣደፈ ውድቀት እና 

በተለይ በአብዛኛዎቻችን ዘንድ የሚታወቀውን 

የእክሰስ ሪል እስቴት ድርጅት 

አጠቃላይ ሂደት በምሳሌነት 

በማስቀመጥ የፕሮጄክት 

አፈፃፀሙን ውስጣዊ እና ውጫዊ 

ዝርዝር ሂደቱን ከመፅሐፉ በግሌ 

ጠብቄ ያጣሁት ክፍል ቢሆንም 


ለንባብ ምቹ ሆኖ ቀለል ባለ አማርኛ 

መቀመጡ ብቻ ሳይሆን 

በዝግታ የተሰናዳ የቃላት ህፀፆች ከሞላ ጎደል የማይታዩበት 

(የሚያስፈሎገውን ገፅ 39) አይነት 

የተልባ ፍንጣሪ ጥቃቅን ስህተቶች 

ከማውጣት ውጭ በሌሎች ዘርፎች የተሰማሩ ባለሙያዎችን 

የሚያበረታታ አርዐያ ሊሆን 

የሚገባው እንደ 'ማንዋል'  ሆኖ የሚያገለግል ሥራ ነው:: 


በየቢሮአችን መፅሐፍ መደርደርያ ልናጣው የማይገባ አገልጋይ መፅሐፍ::  <<ሪስ እስቴት ኢንቨስትመንት አስተዳደር እና ግብይት>>


ተስፋ በላይነህ 

የካቲት 2013 - ኢትዮጵያ!


Jun 9, 2019

መራራ እውነት- በኢትዮጵያ ታሪክ መፅሐፍ ዳሰሳ

ራራ እውነት በኢትዮጵያ ታሪክ መፅሐፍ ቅኝት!!





"ታሪክ ጠላ ቤት ተቀምጦ በጥላቻ ስካር የሚደረስ ልቦለድ ሳይሆን በማስረጃ ላይ ተመስርቶ የሚፃፍ እውነታ ነው::" ገፅ 228:: 


አንድ የመፅሐፍ ወዳጄ ገዝቶ ላከልኝ:: እስክቀበለው ድረስ በጣም ጏጉቼ ስለነበር እጄ ሲገባ ደስ አለኝ:: አለሁበት ቦታ እንደተቀመጥኩ ጀመርኩት:: 100 ገፅ መሆኑን ያወቅሁት ስልኬ ሲጠራ የነበረኝን ቀጠሮ ሳስታውስ ነው:: ቁጭት ነው:: ሃቅ ነው:: የሩብ ክፍለዘመኗን ኢትዮጵያ በመረረ መንፈስ ይመላለስባታል:: የሰው እስትንፋስ እጅግ አስቸጋሪ ኃይል ነው:: እምቅ ጉልበት:: ደፍቶ ይጥላል:: የታጨቀ የዘመን ኩርፊያ:: ያውም የታሪክ ስቅለት የደረሰባትን አገር እዳ መሸከም ቀንበሩ እጅግ የከፋ ነው:: 


"ታሪክ የታመመ ጭንቅላትን ያክማል" የሚባለው የሌቭን አባባል በራሱ ባለታሪኮችን ጭንቅላት በክፉኛ ሳያሳምም አይቀርም:: ምክንያቱም በታሪክ ለመታመም መጀመርያ ሰው መሆንን ይጠይቃል:: ሰው መሆን ደግሞ ጭንቅላት ልብ እና ኅሊና ያለተቃርኖ በስሙሙነት የሚተዳደደሩበት "ሥጋለባሽ ፍጥር" መሆን ነው:: በኢትዮጵያ በሩብ ክፍለ ዘመን ታሪኳ ግን ሶስቱ ዓበይት ውቅሮች ከስጋ ለባሹ ጋር መጣመራቸውን መመስከር ያስቀስፋል:: በታሪክ ስጋ ለባሹ ብቻ በሚከበርባት አገር መፈጠር ህመም ነው!!


ይቺ የማትመቸኝ <<27 ዓመት>> የምትባልን ቃል ላለመደጋገም "ሩብ ክፍለ ዘመን" በሚል ዘይቤ ብወክላት የሚሻል ይመስለኛል::


የመፅሐፉ አዘጋጅ በሥነ ፅሑፍ ስልነቱ አቻ አይገኝለትም:: በየገፁ የተሞሉት የዘይቤያዊ ገለፃዎች ልክ ቁጭ ብሎ እንደሚተርክልህ አይነት ባለታሪክን ይመስላሉ:: ኃያል ነው:: ብእሩ አድምቶ እዛው ፈጭቶ ጋግሮ እንደሚመግብ መና አቅራቢ ነው::


መፅሐፉ ላለፉት ሃያ ምናምን አመታት "ብርሃኔ" ነው ለሚሉት ለስርአቱ አሽከሮች ከሽፋን ገፁ ጀምሮ ሲታይ ገፊ መሆኑ አያጠያይቅም!! ምክንያቱም የኢትዮጵያ ታሪክ ተብሎ አክሱምን አለማስቀመጡ የሆን ተብሎ ሊመስል ይችላል:: የሽፋን ገፁ መራር እውነት ብሎ አፄ ቴዎድሮስን የአበገዳውን ገፅ እና  ድንቅነሽን አጣምሯል:: 



እንደዚህ ፅሁፍ አስተያዬት ሰጭ እምነት መሰረት:: በኢትዮጵያ ታሪክ የተከሰቱ ተቃርኖዎችን በመፈተሽ  የፖለቲካ ንትርካችንን ማከም መቻል የምንጊዜም ታሪክ አዋቂያን አላማ ሊሆን ይገባዋል የሚል ፅኑ እድል ፈንታን ወስዷልና መስለ ስራዎችንም ይሁን ግለሰቦችን አጥብቆ ይሞግታል ይማፀናል ኃቀኝነታቸውን ፈትሾም ይወዳጃል::


መፅሐፉ በ416  ገፆች ተጠርዞ:: አራት አበይት ምእራፎችን ይዞ የኢትዮጵያ ታሪክ ላለፉት አርባ እና ሃምሳ አመታት የደረሰበትን እዥ "ነቀርሳ" ለማከም ይታትራል::  (ነቀርሳ ቫይረስ ነውና ለቫይረስ ህመም ህክምናው ቀላል እንደማይሆን እያሰብን የአካሚውን ተጋድሎ ብርትት እና ቁርጠኝነት ሳናደንቅ አናልፍም)


በምእራፍ አንድ የታሪክ አፃፃፍ ትምህርትን -የታሪክ ምንድርነትን -ማስረጃዎችን የታሪክ አፃፃፍ ጅምሮችን (በተለይምለታሪክ አፃፃፍ ያለን የዘመን ቅርበት) እንዲሁም ዋነኛ የችግሮቻችን ማጠንጠኛ አለት የሆኑትን "የኢትዮጵያ ታሪክ ፀሐፍት ተቃርኖ" በአንደኛው ምእራፍ ወስጥ ተተንትነው ቀርበዋል::


በገፅ 123 የቀረበው የኢትዮጵያ ታሪክ ጸሐፍት ተቃርኖ ክፍል ውስጥ 

ሀ) የቤተ መንግሥት ታሪክ መዝጋቢዎች 


ለ)የማርክሲስት ሌኒኒስታዊ አመለካከት ታሪክ ጸሐፊዎች


ሐ) የዘውግ ታሪክ ጸሐፊዎች በሚል ካስቀመጠ በሁዋላ ለአሁኗ ኢትዮጵያ የችግር ሁሉ ምንጭ ሆኖ የቀረበውን "ዘውጌነት" በአስር ምደባዎች በማስቀመጥ እርቃናቸውን ሳያስቀር አደባባይ ላይ ይገልጣቸዋል:: 


የዘውጌ ታሪክ ፀሐፊዎችን ከኦሮሞ ዘውግ ታሪክ ጀምሮ ኦነግን እንደ ፅንሱ መስራች በመቁጠር መራር እውነት እንጋት ዘንድ ብርቱ ሰይፉን ይመዝዛል:: በዚህ ክፍል ውስጥ ትልቅ ጥናት ውይይት የሚያስፈልገውን የናዚዎች መሸሸግያ ማጣት እና ምሽጋቸውን ኢትዮጵያን የማድረጋቸው ትንተና የዚህን ፅሑፍ አስተያዬት ሰጭውን ቀልብ እና ልቡና የሳበቡት-  የመፅሀፉ 133ኛ ገፅ አንድ ሙሉ መፅሐፍ የሚወጣው እንደሆነም ሳይሸሽግ አያልፍም!!


ከኦሮሞ ዘውግ ታሪክ ፀሐፊዎች ተሻግሮ የትግራይ ዘውገኞችን የሚተነትነው በገፅ 135 ሲሆን የሰሜኗ ኢትዮጵያን ህውሃት መራሽ ኃይል ከደቡቡ ኢትዮጵያ ኦነግ መራሽ ሰይፍ ጥምረት የፀረ ኢትዮጵያዊነት ዘመቻ (በፀረ አማራነት ሽፋን) እና የአለም አቀፋዊውን ደባ መላመት አያይዞ ማቅረቡ አሁንም የዚህን ፅሑፍ አስተያዬት ሰጭ ቀልብ የሳቡት ወቅታዊ ጉዳዮች ናቸው!! 


በትግራይ ዘውጌዎች ርእስ ስር በተደጋጋሚ ሲጠቀስ የምናዬው ፖለቲከኛ/ፀሐፊ አስራት አብርሃም ይህ መፅሐፍ በሚፃፍበት ወቅት የነበረውን አመለካከት ደራሲው ቢፈትሽ መልካም መሆኑን እየገለፅን- በግለሰቦች አመለካከት የዘውግ መዋቅራችን መፈተሹ አልፎ አልፎ ክርክራችንን በውሃ ላይ ቆረቆር እንዳያስብሉብን መጠንቀቅ ሳያሻ አይቀርም:: ፕር ገብሩ ታረቀኝ በጉልህ ተማጋሽ ሆነው የቀረቡበትም ምእራፍ እንዳለ ልብ እንልለን::: 


ከሁለቱ ዘውጌዎች ሌላ  ወደ ሶስተኛው ዘውጌ ተረኛ "አማራ" ዘውግ የታሪክ ፀሐፊያን ያሸጋግረናል:: ፀሐፊው እንደአብዛኞቹ የአንድነት ፖለቲካ አቀንቃኞች "አማራ የለም" በሚል የፖለቲካ አፍ መፍቻ መወድስ አይታወቅም:: 


ለዚህም በቅርቡ በማህበራዊ ድረገፆች የተነበበቡት አጫጭር ፅሁፍ የግል ምልከታዎች "ውሃልክነት እና አማራ የኢትዮጵያ ፈጣሪ..." አባባሎች ፀሐፊውን ክፉኛ እንደነኩት ሳንጠቅስ ማለፍ አይቻልም:: (የዚህን ዝርዝር ምልከታ በሌላ ፅሁፍ ብንመለስበት የሚበጅ ይመስላል)


ቀጥሎም የሶማሊ ዘውገኞችን ከዳሰሰ በሁዋላ በዘመናችን የሚታዬውን የታሪክ ሽሚያም እስከ ቀጣዩ ምእራፍ ድረስ በበላይ ዘለቀ በአፄ ቴዎድርስ በእፄ ኃይለሥላሴ ላይ የሚነሳውን "የዘር" ጥያቄ ግምት ውስጥ በማስገባት ሚዛናዊውን <<መራር እውነት>> በተባው ቁጭት ስሜት ይሞግተናል::


ቀጣዩ ምእራፍ ገፅ 156 የሚጀምረው <<የደማቅ ታሪካችን ሰበዞች>> በሚል ርእስ ነው:: 


ከቅሪት አካል ሳይንሳዊ ግኝቶች "ድንቅነሽ" ጀምሮ ጥንታዊዋን ኢትዮጵያ በዓበይት የታሪክ ምእራፍ አምዶች እየከፋፈለ ፑንትን -ዳእማትን አክሱምን ዛግዌን ሰለሞናዊውን ያስቃኘናል:: ይህ መፅሐፍ ሰለሞናዊውን ስርአት በትእምርተ ጥቅስ ውስጥ ካላስገቡ የታሪክ ድርሳናት ውስጥ መመደቡን  ልብ ብለን እያሰመርን ወደ ሶስቱ የኢትዮጵያዊነት አምዶች <<ዋቄፈና _ክርስትና እና እስልምና>> ሽግግር እንዘምታለን:: ገፅ 169-ገፅ 190::


በተቃርኖ የተሞላው ፖለቲካችን ክምችት የታሪክ አተያያችን እና ግልብ አዘጋገባችን እንደሆነ ይነገራል:: ለዚህም ተቃርኖ መፈጠር ለችግር መዳረጋችን ለመራር እውነት ፍለጋው ለተቃርኖው "ነቀርሳ" ታሪክን በጥልቀት መመርመር ፈውስ እንደሚሆን ታምኗል:: ጥያቄው እነኚህ ተመራማሪ ኃቀኛ ታሪክ አዋቂያን እንዴት ብለው ነው የፖለቲካውን ድር መበጣጠስ የሚችሉት? የፖለቲከኞችን አዙሪት ቀልበው ለሰከነ አስተዳደራዊ መዋቅር የሚያስናዱት? የሚለው ይሆናል::


በኢትዮጵያ ታሪክ ፀሃፍያን እና በኢትዮጵያዊነት የረዥም አመታት ተንታኝ ግለሰቦች ዘንድ የሚጠቀሱትን "አይሁድ-ክርስትና-እስልምና" እምነት ትስስሮችን ወደ "ዋቄፈና-ክርስትና እና እስልምና" መስተጋብር የተገለፀበት መንገድ የፀሐፊው ልዩ ገፅታ ይመስለኛል::  እንደነ ፕሮፌሰር መስፍን የኢትዮጵያዊነት ገለፃ አይሁድ ክርስትናና እና እስልምና የፈጠሩት ውህደት የኢትዮጵያዊነትን መአዛ እንዳሰፈነ ሲገለፅ የኖረውን የታሪክ አተያይ የመምህር ታዬ ቦጋለ መፅሐፉ ግን ስለ ደቡባዊው የኢትዮጵያ ክፍል በተለይ የኦሮሞ ጎሳዎችን ቦረናን እና ጉጂን በድንቅዬ እሴታቸው በገዳ ስርአት ቀለም እያስዋበ ያቀርብልናል:: 


የገዳ ስርዓትን ከአቴንሱ የዴሞክራሲ መነሻነት ጋር በማነፃፀር አቅሙን ይፈትሽልናል:: የግሪኮቹ ዴሞክራሲ ፅንሰ ሃሳብ ከገዳው ስርአት በእድሜም በፍትሃዊነትም በአተገባበርም ሆነ በትርጉም ከቦረኖቹ ጋር ሲመዘን <<በንፅፅር ሚዛን>> ቀልሎም ተገኝቷል:: በአጠቃላይ ይህንን የገዳ ስርአት "የዴሞክራሲ ውሃ ልክ" ሲልም በግልፅ በገፅ 191 በማስቀመጥ እስከ 212 ገፅ ተተንትኖ ቀርቦልናል:: 


ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያዊንትን ከገዳ ስርአት ውጭ ማሰብ እንደማይቻል ደጋግሞ በማስቀመጥ ይሞግተናል:: ከኢትዮጵያም አልፎ በአፍሪቃ እውቅና እና ግልጋሎት ይቸረው ዘንድ   አብዝቶም ይመክራል!!


ፀሐፊው  የኢትዮጵያን ህብረ ቀለማዊ እይታን ሳይሸሽግ የሚመሰክር ነው:: ፅንፈኛ ዘውጌዎችን አጥብቆ ሲሟገት አሃዳዊ ስርአትን ከሚሹት ወገኖች ሊመደብ እንደማይችል "የፖለቲካውን ስፔክትረም" ቀለማት አጥንቶ የተዘጋጄ በመሆኑ ለሃሜት እንዳይዳረግ ሆኖ ራሱን የጦር ልብስ አልብሷል!!


ይህንንም አገላለፅ በፍቱንነት የሚመሰክርልን ኢትዮጵያን ከብሄረሰቦች እስርቤትነት የፖለቲካ ቅኝት ወደ የብሄረሰቦች ሙዝየምነት እና የብሔረሰቦች ሞዛይክነት እንዲሁም ባለ ብዙ ፀጋዎች ሀገርነት (ገፅ209) ስያሜ ማስቀመጡን ልብ ስንል ነው:: 


ሌላኛው ተቃርኖ የአዲሲቷን ኢትዮጵያ የነገስታትቻችንን ታሪክ ቅርፅ ይዘት በጥልቀት መለዬት ጉዳይ ነው:: አፄ ቴዎድሮስ በዘውጌ ታሪክ ፀሐፊያን ዘንድ በተለይም የዘውግ ፖለቲካ መዋቅራዊ ከሆነበት ዘመን ጀምሮ በተጨማሪም እውነት እስኪመስል ድረስ የሚሰበኩት "ምኒልክ ተኮር ዘገባዎች" በዚህ መፅሐፍ ተመርመረው ቀርበዋል:: 


"አባት እሆንሀለሁ ልጅ ትሆነኛለህ:: ጠላት ዙርያችንን ከብቦናል:: አንድነታችንን እናጠናክር:: ሠራዊቴ ኃያል ስለሆነ ብትገጥመኝ ወገን ታጨራርሳለህ:: በሰላም ለእኔ አድረህ ገብር:: ራስህን በራስህ ታስተዳድራለህ:: በውስጥህ ጉዳይ ጣልቃ አልገባም::" 

የሚለው አባባል ለፌዴራሊስቶቹ ጭንቅ የሚሆን ነው:: "ራስህን በራስ ታስተዳድራለህ" የሚለው ስንኝ ለዘመነኛ ፌዴራሊስት ነን ባዮች (ስሁታዊያን) ከማን አፍ የወጣ ቃል ነው ተብለው ቢጠየቁ ወደ ምኒሊክ የሚያተኩር ልእልናውን አልፈጠረባቸውም::  


በኢትዮጵያ ታሪክ ከመራሩ እውነት አንደኛው "የታላቁ ተቃርኖ" ምእራፍ መግቢያ የምኒሊክ ጉዳይ ነው:: ምኒሊክን እንደ አቅላጭ/ አሃዳዊ መሪ ሳይሆን እንደ ፌዴራሊስት መሪ እንዲሁም እንደ ጨቋኝ ሳይሆን እንደ ነፃ አውጭ መሪ መውሰድ የታዬ ቦጋለ ብእር ቋሚ ተማጋች ነው:: 


እንዲህ አይነቱን መራር እውነት መጋት ግድ ሳይል አይቀርም:: የመፅሐፉ አቅራቢም ኦሮሞን በገዳ ስርአት እሴቱ በኢትዮጵዊነት ማማ ላይ ቋሚ አምድ የማድረጉን ያክል አፄ ቴዎድሮስ እና አጤ ምኒልክን ጉልህ አሻራነት ለድርድር ሳያቀርብ የተለመድ ዝናሩን ያበረታል!! ፀሐፊው በዚህ ብርታቱ እውነትን ተናግሮ እመሸበት ማደርን ብሂል ሊተገብር ላይ ታች ሲልም ይስተዋላል:: 


ልጅ እያሱ -ንግስተ ነገስታት ዘውዲቱ እና ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ በበጎነታቸው ሚዛን ላይ ሲቀመጡ የደርግ እና በተለይ የቀጣይ 1983ቱ ስርአት በዘመነ ፅልመት ስያሜነታቸው ተከትበው እናነባለን:: 


ይህ የአዲሱ ዘመን ታላቁ ተቃርኖአችን ነው:: ከ1966 እስከ አሁን በተልይም ከ1983 ወዲህ ኢትዮጵያ ነፃ የሆነችበት የብርሃን ዘመን ወይንስ እንደ ፀሐፊው አባባል ዘመነ ፅልመት?


በቀጣይ የምንዳስሰው ይሁን:: ምናልባትም የታሪክ መምህራን (ምሁራን) በዚህ ክፍል ላይ የሰላ ትኩረታቸውን ቢሰጡበት እና ኢትዮጵያችንን ከእንቅልፏ ከድንንዛዜ ከነቅርሳዋ ያክሟት ዘንድ ቅን ባለሙያዎችን እና ጋሻ ጃግሬ ባለሟሎች የምትሻበት የዘመን ምእራፍ ላይ እንገኛለን:: 


የዚህ ፅሑፍ ፀሐፊ ባለሙያ ሳይሆን የባለሙያዎች ባለሟል:: የኢትዮጵያዊነት ጋሻ ጃግሬነቱን እድል ፈንታን በመውሰድ አሁንም ከንባብ ከሃሳብ ከመሰል ተሳትፎነት ሌት ተቀን አይቦዝንም:: 


ስጋለባሽ ከሶስቱ መዋቅሮች ጋር ትሥሥር አለው ብሎ ያምናልና!! ለዚህም አይነት ፍጡር ታሪክ አኪሙ ነው:: አካሚዎችን አያሳጣን እያለ ለጊዜው ይሰናበታል!!