May 17, 2016

ኢትዮጵያ ምን አይነት አስተዳደር ያሰፈልጋታል?


"Mother Ethiopia" by Aleka Gebre Selassie Adil"s (1881-1975)


-1-


ይሕ ርዕስ የመጨረሻው ይመስለኛል፡፡ አሁን እየጦዘ ባለው እና ዳር ቆመን እየተከታተልን ለምንገኝ ‹‹አገር እና ሕዝብ ያስጨንናል‹‹ ለምንል ተራ ግለሰቦች፤ የመጨረሻው ጥየቄ የሚወድቀው በዚህ ርዕስ ትከሻ ላይ ይመስለኛል፡፡ ኣንዳንድ ጸሐፊያን የትላንቱን እና የዛሬውን አጢነው የነገውን ሲመነዝሩ ሲታዩ፤ የሚሠማቸው እጥተው በየገጾቻቸው ባክነው የቀሩት የፊደል እና የሐሳብ ዘለላዎች፤ ‹‹ነብይ ባገሩ አይከበርም…›› እንደሚያስብለን የታመነ ነው፡፡ ሐዲስ አለማየሁ ነብሳቸውን ይማርና በዚህ ርዕስ ጉዳይ መጽሐፍ አሳትመው አቅርበውልናል፡፡ በተለይ ለሕትመት የበቃበት ወቅቱ የየምድር ጦር እና የፖሊስ ሠራዊት ቡድን /ጦር ኃይሎች ደርግ/ ማቆጥቆጥ ሲጀምር፤ “የበለሷ ዛፍ ስታቆጠቁጥ መከር መድረሱን እወቁ..” እንዲል መጽሐፉ፤ እነ ሐዲስ አለማየሁም የበኩላቸውን ሐሳብ አደርሱ፤ ከመከር በፊት፡፡ ሰሚ የጡት ነብያትም እንደ ቁራ ጮኸው ቀሩ.. ደርግም ከማቆጥቆጥ አለፎ አበበ፡፡ አብቦም ፍሬው የዙፋን ጠረጴዛ ላይ ደረሰ፡፡ ዙፋን እንደ ጠረጴዛ የደም ሻምፓኝ ፈሰሰበት፡፡
ከሞላ ጎደል ሀዲስ አለማየሁ የተናገሩት ሁሉ እንደ ትንቢት ሆነ ተፈጠመ፡፡ መስፍን ወልደማርያምም በዚህ ሐሳብ ላይ የበኩላቸውን አስተያዬት አዘል መጽሐፍ ለሕትመት አብቅተው ነበር፡፡ ኢትዮጵያዊነት ልማት በሕብረት በሚል ርዕስ፡፡
ጽድቀ-ደራሲ እንዳለ ጌታ ከበደ ምስጋናዬ ይድረሰውና በዚህ ርዕስ ዙሪያ ሐሳቤን አቅርቤለት፤ መሠል መጽሐፍቶች ተጽፈው እንደሆን ጠየቅሁት፡፡ እንዳለ ጋር ጣጣ የለም፤ ‹‹ይድነቃቸው ተሳማ መንግስትና አስተዳደር፤ ዮሐንስ ገ/ጻድቅ/ የምንዱባን ተርጓሚ/ እንዲሁም ከቀድሞዎቹ ነጋድራስ ገ/ሕይወት፡፡ ተያያዥነት ያላቸውን ርዕሶች ይዘው መጽሐፍ ጽፈዋል›› ተያይዞም ሶስት ምሑራን በፕ/ር መስፍን መጽሐፍ ላይ አስተያየታቸውን እንደሰጡ ገለጸልኝ፡፡ ምናልባት አዲስ ዘመን አሊያም የዛሬይቱ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ላይ ታገኘዋለህ፤ 66 ዓ.ም እትም፡፡ ወደ ወመዘክር አቀናሁ፡፡ በቃ እንዳለ እንዲህ ነው፡፡ የተባሉትን መጽሐፎችንም ሆነ የጋዜጣውን እትም አገኘሁት፤ የዛሬይቱ ኢትዮጵያ 1966 ዓ.ም ነሐሴ እትም ላይ፤ ፈቃደ አዘዘ፣ ዮሐንስ አድማሱ፣ እጨቱ ጮሌ ሆነው የጻፉትን አገኘሁ፡፡ ማለፊያ፡፡
ምናልባትም ይሕንን ጉዳይ በጥልቀት ለመተንተን እና ወደ መዳረሻ ሐሳብ ለመቅረብ ምሁራኑን ማነጋገር ነበረብኝ፡፡ በአጸደ ሥጋ የሚገኙት ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ ላለፈው ታሪክ ጥናት በእጅጉ ከሚጎዱት ተሰንቃሪ ምክንያቶች ውስጥ አንዱ ‹‹በአጸደ ሥጋ አለመገኘት›› ነው፡፡ ፈቃደ አዘዘ /አሁን ፕ/ር/ በሕይወት ይገኛል፡፡ እሱንም አግኝቶ ለማነጋገር ቀላል አልሆነልኝም፡፡ ብዙ ሰዎችን አላውቅም፡፡ በዙ ሰዎችን አለማወቅም ሌላኛው የጥናት ስራ እንቅፋት ነው፡፡ የማውቀቸውም ሰዎችን እየደጋገሙ ማስቸገር ቀላል የማይባል ጋሬጣ ነው፡፡ ፕ/ር መስፍን ጋር ወደልክሁ-ሁሌም በራቸውም ስልካቸውም ክፍት ነው፡፡
 ‹‹በዛሬይቱ ኢትዮጵያ ላይ በወጣው ኢትዮያዊነት ልማት በሕብረት መጽሐፍ ላይ አስተያዬት በሰጡት ምሁራን ላይ አስተያዬት አልዎት? በወቅቱስ ምላሽ የሰጡበት ቦታ አለ?›› ጠይክኋቸው፡፡
‹‹ሲጀመር አስተያዬቱ ሙሉ በሙሉ ሥለመጸሐፉ አያወራም፡፡ መጽሐፉ ላይ አነጣጥሮ የተሰነዘረም አልነበረም በዚህ ምክንያት አስተያዬት መስጠት አይቻልም…›› መለሱልኝ ፕሮፌሰሩ፡፡
ግራ የሚገባ ነገር ነው፡፡ ቁጭ ብለን የተመካከርንብት ጊዜ አልታይሕ አለኝ፡፡ ምሁራኖቻችን በጋራ መድረክ፤ የግልም የጋራም ሐሳቦቻቸውን የሚሠነዝሩበት፣ መንጋውን የሚገሩበት መድረክ ፈጽሞ የለንም፡፡ አሁን ላለንበት የፌስ ቡክ መልስ ምቶች እና የየግላችን ሐሳቦች ቁርቁዝ አመላካች ገተመኞቻችን ናቸው፤ ምሁራኖቻችን መስመር ስላላበጁለት፤ ተቀምጦ የመዋየት ባሕል ስላላዳበሩልን፤ሁሉም በያሻው ያሸ ያሻውን ይወረውራል፡፡
 በአንድ ታሪክ ላይ ሕልቆ መሣፍርት መልስ ምቶች እና አለመግባባቶች አሉብን፡፡ ይሕ መዳረሻ አገር አይገነባም፡፡ እንኳን አገር ድልድይ አይጠግንም፡፡ የትም አያደርሰንም፡፡ ለተወሰነ ጊዜ ከፌስ ቡክ የራቅሁበት ምክንያትም ይሕ ነው፡፡ ሁሉም የያሻውን መጻፉ ባልከፋ፤ ነገር ግን ሁሉም ያለመደማመጥ ሲያወራ፤ ላለመግባባት ጀምዓውን ሲያደነቁር ቢውል ለስጋም ለነፍስም ሕመም ነው፡፡
ኢትዮጵያ ምን አይነት አስተዳደር ያስፈልጋታል?  የኔ መዳረሻ ጥያቄ ይኄው ነው… እንወያይበት!!
/ተስፋ በላይነህ፡ ግንቦት 20/2008/

No comments: