Sep 1, 2015

የተስፋ ክትባት! በዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፡፡



የተስፋ ክትባት! በዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፡፡
ተስፋ በላይነህ    



‹‹የተስፋ ክትባት›› የባለ አስራ ሰባት ገጽ መግቢያ አዘል፤ ነሐሴን 2007ዓ.ም  ሳንጨርስ 2008 ዓ.ም ስር የተመዘገበች የባለ 100 ገጽ የግጥም መድብል ነች፡፡ በ45 ብር፡፡
በድሉ ዋቅጅራ(ዶ/ር) አምስት ስራዎችን እንዳቀረበልን ከመጽሐፏ የሽፋን ጀርባ ላይ ማዬት እንችላለን፡፡ በተማሩበት የትምሕርት ዘርፍ፣ ባስታመረው ሕብረተሰብ ሕመም እና ደስታ ማዕድ ሥር ሆኖ፤ ማሕበረሰብን መከርከም፣ መንገድ መምራት እንዲሁም የልቡን ሕመም መጋራት፣ አልፎም መጻፍን የመሰለ ክብር ያለ አይመስለኝም! አለ ብዬም መሟገት የሚያስችል አቅም አይኖረኝም፡፡ በርታልን ዶ/ር ከማለት ውጭ!!
የጥልቅ ምናብ ባለቤት
‹‹የተስፋ ክትባት›› በመግቢያዋ ሥለ ግጥም መባል የሚገባቸውን፤ አንኳር ነጥቦች አንግባ፤ 43 ግጥሞችን ተሸክማለች፡፡ በመግቢያው እንደተገለጸልን ሃያሲ እንደ ገጣሚው የጥቅል ምናብ ባለቤት መሆን ይጠበቅበታል በሚል እውነታ፤ ይሕችን የግጥም መድበል ለማሄስ ራሴን ጠየክሁት፡፡ የጥልቅ ምናብ ባለቤት ነኝን? ሥል፡፡
የጥልቅ ምናብ ባለቤት መሆኔን ለመረዳት፤ ጥልቅ ምናብ ያላቸውን ገጣሚዎች ስራ ፈልጎ ማግኘት እናም አንብቦ መረዳት በራሱ አመሳካሪ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ሥለዚህ የተስፋ ክትባትን ከገጽ 23-100 ማንበብና መረዳት፤ ከዚያም የጥልቅ ምናብ ባለቤት እኔ ወይንስ ገጣሚው በሚል ኃልዮት ለማንበብ ፈቀድክሁ፡፡
የውበት ፍጽምና መታደል፣ ለምናባዊ ፍጽምና መቅረብ ከዛም ቃላትን፣ እየገጣጠሙ፣ ምሳሌዎችን፣ ዘይኔዎችን፣ ፈሊጦችን..   ቋንቋ የፈቀደለትን በሙሉ በመጠቀም፤ የምናቡን ስዕል ለአናባቢው ለማሳየት መሞከር ከዚያም በስተመጨረሻ ምናባዊ ምስሉ ገሀዳዊ ህልውና እስኪያገኝ ድረስ የሚደከንበት ስራ ነው- ግጥም!...ገጽ 22፡፡
እዚህ ላይ መስማማት ያለብን ነገር ቢኖር፤ የገጣሚው የጥልቅ ምናብ ባለቤትነት፤ የአንባቢውንም ምናባዊ ጥልቀት መፈተሹ እና ትስስራቸው የተደጋገፈ መሆኑን ማወቅ ነው፡፡ ገጣሚው ጥልቅ ምናብ ባለቤት ከሆነ፤ አንባቢው (በስፋት ሃያሲው) ምናቡን ሊያሰፋለት መቻሉንና መደጋገፋቸው ትልቅ ኃይል መሆኑን በማሳሰብ ወደ ግጥሞቹ እናዝግም፡፡ የአንበሳውን ድርሻ የሚወስደው ምናቢ ጥልቀት ኃይል ግን ከገጣሚው እንደሚጠበቅ ሳንስማማ አናልፍም
ግጥሞቹ ለኑሮ ጓደኛ፣ ለማሕበረሰብ ድንቁርና፣ ለሴት ልጅ ስሜት፣ ለቤተሰብ፣ ለአገር እንዲሁም ለፖለቲካ ምልከታ ውለው፤ አጋጣሚዎችን ተገን አድርገው የተጻፉ ይመስላሉ፡፡ እያንዳንዱ ግጥሞች በመቼት እና በቦታም ተሰድረዋል፡፡
በግሌ የግጥም ምናባዊ ጥልቀት ወደ ተጨባጭ የወግ፣ የሥርዓት እና ተፈጥሮአዊ ይዘት ውስጥ ሆነው የምኖረውን ሕይወት ባልተመለከትኩበት ማዕዘን እና ስሜት የተጻፈ ሲሆን ቀልቤን ይስበዋል፡፡ ምናቤን ያጎነዋል፡፡ ነፍሴን ያሾራታል፡፡ ጥልቀቴን እንደ ጅረት ውሃ ድምቀት እያስዋበ ትስፍህት ዜማ ሊያሰማኝ ይጋባል፡፡
ሆኖም ወደ ምናባዊ ጥልቀት ውስጥ መግባት ቀላል ጉዞ አይደለምና፡፡ ምንባዊ ጥልቀት ዝም ብሎ ተነስቶ የደርሶ መልስ “ትኬት” ቆርጦ እንደመጓዝ አይነት ጉዞ አይደለም፡፡ ወደ ጥልቁ ለመጓዝ ስናስብ የጉዞውን ርቀት፣ ስፍር በተለይም መመለሻ ባቡሩን ማሰብም የሚጠበቀው ከአንባቢ ነው፡፡ አንባቢ ልክ እንደ ተሳፋሪ ነው፡፡ መሪውን የያዘው ገጣሚው (ጸሐፊው) ከሆነ፤ ተሳፋሪ በፈለገበት መንገድ መጓዝ እይችልም፡፡ የመንገዱ አቅጣጫ የሚወሰነው በባለመሪው መዳፍ ስር ነውና! ጥንቃቄው የትየለሌ ነው፡፡ ሆኖም ተሳፋሪው ዋና መቻል አለበት፡፡ መዋኘት ከመቻልም ባሻገር የቅድመ ደህንነት ትጥቁን ማሟላት አለበት፡፡  ወደ ጥልቁ ተጉዘው መመለስ አቅቷቸው አቅጣጫቸው ጠፍቶባቸው ሲመላለሱ የምናያቸው፤ ጥልቁን የሕይወት ውቅያኖስ መሻር አቅትቸው ሲዋልሉ የቀሩት ጥቂቶች አይደሉምና!!
በበኩሌ ግጥሞቹ አነስተኛ ገላጭ ስዕሎች ቢታከሉበት የትየለሌ ምናባዊ አድማሳችንን ከማስፋታቸውም ባሻገር፤ ውበት ፈላጊ አንባቢን የልቡን ስፋት፣ የነፍሱን ጥማት ያበዙለታል ብዬ እገምታለሁ፡፡(“ኗሪ አልባ ጎጆዎች”  ልቤ ላይ የቀረኝ ውበት)
ገጣሚው ለእድር እና ለአድባር መጨነቁ፤ በዚህ ስራው ብቻ አይደለም አየምናውቀው፡፡ በቀደምት ስራቹም ሆነ በየመጽት መጣጥፎቹ ‹‹አገር ማለት ሰው ነው›› አይነት ፈሊጥ አራማጅ በመሆኑ፤ እዚህ ስራ ላይም ተደጋግሞ መመልከት እንችላለን፡፡ ‹‹ለየቅል አደርን››ን ዋቢ ማድረግ እንችላለን፡፡
እንደ ጥንት መርከበኛ፣ የጊዜ መስፈሪያ አሸዋ፣
አለ ስንለው ተንሸራቶ፣ ፍቅራችን እንሰተሰዋ፤
ልብህ እያወቀ፣ ሹክ ሳትለኝ፣
ልቤ እያወቀ ፣ ሳላጫውትህ፤
እኔም ከአድባር መገለሌ፣
አንተም ከእድሬ መውጣትህ፡፡
አይቆጭህም?!
አሁንም ገጣሚው በየዕለት የሚያጋጥመንን ታሪክ ቀረሽ ምልከታዎች በግጥሙ ክታብ ይጣባናል፡፡ ‹‹ዮሀንስን ናፍቆት›› በምድረበዳ አጥማቂውን ሲያስናፍቀን፤ በምደረ ባዳ ደግሞ
አይገራ ትውልድ፣ አንድ ዮሀንስ ወዶ፤
ከተማው ጭር አለ፣ ምድረ ዳ ወርዶ፡፡ ሲል ከአድማሱ ይሰርቅልናል፡፡
ከአገዛዞቻችን ጋር ግብ ግብ የሚገጥምበት የግጥም ስንኞችን ጥቂት አይደሉም፡፡
‹‹ምስጋና›› ገጽ 76
ገዥያችን ተመስገን!!
እንደፍርሃታችን፣
ኮርቻ ጭነህ ያላጋለብከን፤
እንደሆዳምነታችን፣
ስብእናችንን ገፈህ፣ ከከብት ጋጣ ያላኖርከን፤
እንደተገዥነታችን፣ የጸሎት ቤታችንን ንደህ፣ መመለኪያህን ያላቆምክ፤
እንደአለመጠየቃችን፤
እንበላነት ዘንድ ፈቅደህ፣ አፋችንን ያለጎምክ፤
ተመስገን!!
(ምን ቀረው ባይ ነኝ- የሙስሊሙ ሕብረተሰብ ድምጽ ምን ሆነና-??)
‹‹ኑ ሀውልት እንስራ››
‹‹አንድም በድንቁርና አንድም በእሳት››
‹‹የበደሌን ሀውልት››
‹‹ስም አወጣህልኝ አሉ….›› እና የመሳሰሉትን መጠቆም እንችላለን፡፡ በተለይ ደግሞ የኢህዴግን ፌዴራሊዝም በጣት ተቆጣሪ ስንኞች፤ እንደ አጭር ቁምጣ ልብስ ሲጠቅማቸው እናያለን፡፡
‹‹ለኢህአዴግ››
ጨለማዬን ልትገፍ፣ የለኮስከው ሻማ፣
ተስፋ መድረሻዬን፣ በወንዜ ካጠረው፣
ነጻ ተፈጥሮዬን፣ ቋንቋዬ ካሰረው፣
ልንጓዝ ወደፊት፣ የጠረከው መንገድ
ጉዞ ሳንጀምር፣ ጠቦ ካጫረሰን፣
ተራመድን ስንል፣ ኋላ ከመለሰን፣
ጎዳናው እጅግ ጠቦ፣ ጨለማው ከሰፋ
ወይ መንገድክን ቀይር፣ ወይ ሻማህን አጥፋ፡፡ ገጽ46

 ‹‹ተስፋሽን ፈራሁት›› ግሩም እይታ የታየበት፤ በሴቶች ላይ የሚደርሰውን ጥቃት እና የወደፊት ፈንታችንን የሚያሳይ ምናባዊ እይታ ነው፡፡
    እንዲህ እንዲህ እያለ ረጃጅም ግጥሞችን ይዞ ይዘልቃል፡፡ አንባቢ በትኩረት አይቶ እንዲጋብዝልኝ በመቃኘት እኔም ጽሑፌን ልግታ፡፡
ገጣሚው ከ2003ዓ.ም እስከ 2005 ዓ.ም ወጡ የግጥም መድብሎችን በመቃኘት የግል ጥናት ማድረጉን ነግሮናል፡፡ ከሰባ አምስት በመቶ በላይ የሚሆኑትም “ከመጥፎ ግጥም የሚመደቡ” ሲል ደምድሟል፡፡ ‹‹የተስፋ ክትባት›› ለአዲሱ የጥናት ስራ ራሷን አጋልጣ ብቅ ብላለች፡፡ ከመጥፎው ከጥሩው ናት-? አንባቢና ሃያሲ ይክረምባት፡፡
ዶ/ር በድሉ የአማርኛ ፊደላት ይቀነሱ ከሚለው የምሁራን ወገን ይመስለኛል፤ ይሕንንም በስነጽሑፍ/ሥነጽሑፍ ቃል እና መሰል ቃላት(አለም/ዓለም…) ውስጥ ፈልገን ማግኘት እንችላለን፡፡ ሥነ- ማለት ‹‹ጥናት›› ወይም ‹‹ውበት›› ማለት ሲሆን ስነ ሲሆን ግን ‹‹ጥርስ›› ማለት እንደሆነ የግዕዝ ልሒቃን ሲነግሩን እንመለከታለን፡፡ በዚህም ጉዳይ ትልቅ ውይይት እና መፍትኄ እንደሚያስፈልገው የሁላችንም ፍልጎት እና ምኞት ነው፡፡
የመጨረሻው ረዥም ግጥም ተደጋጋሚ ገጾችን ከመያዙ በቀር፤ እንዲሁም የግጥሞቹ ቁጥር ማነስም በቀር ያስተዋልሁት ደቂቃን ሕጸጾች አልነበሩም፡፡ ለተደራሲው መልካም ንባብ! ለደራሲውም ሌላ ማለፍያ ሥራ፤ ከጥልቀት ምናባዊ እይታ ጋር!!
ቸር፡፡

No comments: